ኦነግ “በምዕራብና ደቡብ ኦሮሚያ ለተፈጠሩ ችግሮች ተጠያቂው የጠቅላይ ሚኒስትሩ መንግስት ነው” አለ፡፡
በጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የሚመራው መንግስት በኦሮሚያ ክልል በምዕራብና ደቡብ ዞኖች እየተፈጸመ ላለው “እሮሮና ሰቆቃ” ተጠያቂ ነው ሲል የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ከሰሰ።
“ይሄ ችግር በአስቸኳይ ካልተገታ በስተቀር ከዚህም ወደ ባሰ ሁኔታ አድጎ ከማንም ቁጥጥር ውጭ ሊሆን እንደሚችል ስጋታችን እየጨመረ መሆኑን በድጋሚ አስረግጠን ልንገልጽ እንወዳለን” ሲል በመግለጫው ያካተተው ኦነግ “ሆን ተብሎ በዶ/ር ዓብይ አህመድ የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስት በሰላማዊ ህዝባችን ላይ እየፈጸመ ያለዉን ይህንን እሮሮና ሰቆቃ እጅግ አጥብቀን እናወግዛለን” በማለት እንዲቆም ጥሪ አቅርቧል።
መንግስት በኦሮሚያ ምዕራብ ወለጋ ዞኖች የስልክና ኢንተርኔት አገልግሎቶችን አቋርቷል ያለው ኦነግ ‘’የመንግስት ወታደሮችና ታጣቂዎች በሰላማዊ (ትጥቅ አልባ) ዜጎች ላይ እያካሄዱ ባሉት ግድያ የሰዎች ህይወት እንደ ቅጠል እየረገፈ መሆኑ” መረጃ እንደ ደረሰው የሚያትተው ጥር 23 ቀን 2012 ዓ.ም የወጣው የኦነግ መግለጫ በተለይ በምዕራብና በቄለም ወለጋ እየተፈጸመ ያለው “ግድያና ጭፍጨፋ” በቃላት መግለጽ አዳጋች ነው ብሏል፡፡ በዚህ ሳቢያም ድርጊቶቹን የሰብአዊ መብት ጥሰትና የጦር ወንጀል የሚሉ ሃረጎች ሊገልጿቸው አይችልም ሲል በመግለጫው አስታዉቋል፡፡
ስለዚህም የተጠቀሱት ችግሮች ተቀርፈው መፍትሄ ይመጣ ዘንድ “በግድያና ጭፍጨፋ በእስራትና በማንኛዉም መንገድ በሰላማዊ ዜጎች ላይ በመንግስት እየተካሄደ ያለው ይሄ እሮሮና ማሰቃየት በአስቸኳይ እንዲቆም ይሄንን እያካሄዱ ያሉት የመንግስት ሃይሎች ወደ ካምፕ እንዲመለሱ፤ ያሉት ችግሮች በዉይይትና በሰላም መፍትሄ የሚያገኙበትን ሁኔታ መንግስት እንዲያመቻች፤ ከዚህ ለመሸሽ የተገደዱ ሰዎች ወደ ቀያቸው ተመልሰው ሰላማዊ ኑሮአቸዉን እንዲኖሩ፤ ከደረሰባቸው ጉዳት የሚያገግሙበት እገዛም እንዲደረግላቸው፤ እንዲሁም እየደረሰ ያለዉን ጉዳት በነጻና ገለልተኛ አካል አስፈላጊ ዓለማቀፍ ምርመራ እንዲደረግ፤” ሲል ጥሪ አቅርቧል፡፡
ይሄንን ጉዳይ በሚመለከት ሰኞ ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ጥያቄዎች የቀረቡላቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ምላሽ በምዕራብና በጉጅ ኦሮሚያ ዞኖች እየተካሄዱ ያሉ የመንግስት ዘመቻዎችን አረጋግጠው በጉጂ ዞን ያለው ከአካባቢው አባ ገዳዎች ጋር በተደረገ ዉይይት ቀንሷል ብለዋል፡፡ በምዕራብ ኦሮሚያ ዞኖች ደግሞ ኢንተርኔትና ስልክ መቋረጡን ገልጸው መንግስት በአካባቢው እየተደረገ ካለው ዘመቻ ጋር እንደሚገናኝና በቅርቡ መፍትሄ እንደሚያገኝም አስታዉቀዋል፡፡
በምዕራብ የኦሮሚያ ዞኖች በተለይ ክልሉ ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጋር በሚያዋስንባቸው አካባቢዎች የታጠቁ ሃይሎች የሚንቀሳቀሱ እንደሆነ የሚታወቅ ሲሆን፤ የበርካታ ዜጎችና የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች የሚገደሉባቸው ስፍራዎችም ናቸው፡፡ በቅርቡም ታግተዋል የተባሉ ነገር ግን መንግስት በማን፣ የት እና መቼ እንደታገቱ ሊገልጽ ያልቻለው የደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ጉዳይም የዚህ አካባቢ አንዱ የቅርብ ክስተት ነው፡፡
ብሩክ አብዱ
ምንጭ፡ ሪፖርተር ጥር 27 ቀን 2012 ዓ.ም